1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የረቡዕ መስከረም 1 ቀን፣ 2017 ዓ.ም የዓለም ዜና

ረቡዕ፣ መስከረም 1 2017

https://p.dw.com/p/4kWLV

*የ2017 አዲስ ዓመት መለወጫ ርእሰ አውደ ዓመት ዛሬ በኢትዮጵያውያን እየተከበረ ነው ።  በሀገር ቤት ውስጥ እና አሜሪካን ጨምሮ በተለያዩ የውጭ ሃገራት የሚኖሩ ኢትዮጵያውያን በዓሉን የተቸገሩን በማሰብ እና በመርዳት ጭምር አክብረዋል ።

*በምስራቅ አፍሪቃ የአሜሪካ ልዩ ልዑክ ማይክ ሃመር ዛሬ በኢትዮጵያ አዲስ ዓመት ከትግራይ ክልል ጊዜያዊ አስተዳደር ምክትል ፕሬዚደንት ጄኔራል ጻድቃን ገብረትንሳኤ ጋ ፊት ለፊት ተነጋገሩ ።

*የአማራ ክልል መስተዳድር ምክር ቤት በክልሉ ማረሚያ ቤቶች የሚገኙ 1430 እስረኞች በይቅርታ እንዲፈቱ መወሰኑን የክልሉ ፍትሕ ጽ/ቤት ዐሳወቀ ። 

ዜናው በዝርዝር

አአ፥ የ2017 አዲስ ዓመት በኢትዮጵያውያን እየተከበረ ነው

​የ2017 አዲስ ዓመት መለወጫ ርእሰ አውደ ዓመት ዛሬ በኢትዮጵያውያን እየተከበረ ነው ።  በሀገር ቤት ውስጥ እና አሜሪካን ጨምሮ በተለያዩ የውጭ ሃገራት የሚኖሩ ኢትዮጵያውያን በዓሉን የተቸገሩን በማሰብ እና በመርዳት ጭምር አክብረዋል ። በአንዳንድ የሀገሪቱ ክፍሎች የሚገኙ ተፈናቃዮች ግን ለበዓሉ ምንም የተለየ ነገር አለማግኘታቸውን  ገልጠዋል ። አዲሱ ዓመት በጾምና በሥራ ቀን በመዋሉ በአብዛኛው በአሉ በተለይ የሚከበረው ከነገ ጀምሮ በተለይም ቅዳሜና እሁድ መሆኑ ተገልጿል ። ከዋዜማው ጀምሮ በተለያዩ ዝግጅቶች እየተከበረ በሚገኘው የዘመን መለወጫ ኢትዮጵያ ውስጥ ሰላምን እንዲሰፍን በርካቶች ምኞታቸውን አንጸባርቀዋል ።

 A በምስራቅ አፍሪቃ የአሜሪካ ልዩ ልዑክ ማይክ ሃመር ዛሬ በኢትዮጵያ አዲስ ዓመት ከትግራይ ክልል ጊዜያዊ አስተዳደር ምክትል ፕሬዚደንት ጄኔራል ጻድቃን ገብረትንሳኤ ጋር ፊት ለፊት ተነጋገሩ ።  በትግራይ ክልል ዘላቂ ሰላም ለማስፈንም የፕሪቶሪያ ስምምነት ሙሉ ለሙሉ በአፋጣኝ የመተግበሩ እጅግ አስፈላጊነት ላይ ሁለቱ መስማማታቸውን የአሜሪካ ኤምባሲ ገልጧል ። ሁሉም ኢትዮጵያውያን በሰላም መኖር ይገባቸዋል ከሚለው የኤምባሲው አጠር ያለ የፌስቡክ መልእክት ጋር ማይክ ሐመር እና ጄኔራል ጻድቃን ጎን ለጎን ቆመው የሚታዩበት ፎቶም ይታያል ። ማይክ ሃመር እስከ ፊታችን ቅዳሜ በአዲስ አበባ እንደሚቆዩ ተገልጧል ። ልዩ ልዑኩ በኢትዮጵያ ቆይታቸዉ፦ ከኢትዮጵያ ባለሥልጣናት ጋርም እንደሚወያዩ ተጠቅሷል ። አምባሳደሩ በቆይታቸው በአማራ ክልል የሚካሄደዉን ጦርነት ብሎም በኦሮሚያ ክልል የሚታየዉን አመጽ በዉይይት ለማስቆም ጥረት ያደርጋሉ ተብሏል ። በሌላ በኩል፤ የትግራይ ክልል ጊዜያዊ አስተዳደር ርእሰ መስተዳድር ጌታቸው ረዳ ከልዑካናታቸው ጋር አዲስ አበባ እንደሚገቡም ቀደም ሲል ተዘግቧል ።

ባሕር ዳር፥ በሺህዎች ለሚቆጠሩ እስረኞች ምሕረት

የአማራ ክልል መስተዳድር ምክር ቤት በክልሉ ማረሚያ ቤቶች የሚገኙ 1430 እስረኞች በይቅርታ እንዲፈቱ መወሰኑን የክልሉ ፍትሕ ጽ/ቤት ዐሳውቋል ።  የክልሉ መንግስት በወሰነው መሰረት 1389 ወንዶችና 41 ሴቶች ከዛሬ መስከረም 1 ቀን፣ 2017 ዓ ም ጀምሮ ይቅርታ ተደርጎላቸዋል ተብሏል ። ይህንንም የጽ/ቤቱ ምክትል ኃላፊ አቶ ወንዳቸው ሠራው  ለጋዜጠኞች በሰጡት መግለጫ ገልጠዋል ።

«በ2017 ዓመት የአንደኛ ዙር የይቅርታ ምክንያት በማድረግ በክልሉ የይቅርታ መስፈርት አዋጅ 136/1998 እና ይህን ለማስፈጸም በወጣው መመሪያ ቁጥር 30/2010 መሠረት ለወንድ   1389፣ ለሴት 41 በድምር  ለ1430 በክልሉ ማረሚያ ቤት ለሚገኙ ታራሚዎች ከመስከረም 1 ቀን ጀምሮ ከእስር እንዲለቀቁ ተወስኗል ።»

የይቅርታው ተጠቃሚዎች በሕግ ይቅርታ የማይከለክላቸው፣ የተፀፀቱ፣ ዝቅተኛውን የእስራት ጊዜ ያጠናቀቁ እና እረቅ የፈጠሙ መሆናቸውንም ኃላፊው ተናግረዋል ። የአማራ ክልል ማረሚያ ቤቶች ኮሚሽን የሕዝብ ግንኙነት ኃላፊ ኮማንደር ዓባይ በላይ ይቅreታ የተደረገላቸው ታራሚዎች ከባህር ዳር ከሌሎች ማረሚያ ቤቶች ዛሬ ከጠዋት ጀምሮ እየወጡ ስለመሆናቸውም ተናግረዋል ሲል ዓለምነው መኮንን ዘግቧል ።  በተያያዘ ዜና፦ የኢትዮጵያ መከላከያ ሰራዊት «በክህደት ወንጀል» የጥፈተኝነት ብያኔ ተላልፎባቸው በእስር ላይ የነበሩ 178 የትግራይ ክልል ተወላጅ  ወታደሮች በይቅርታ መለቀቃቸውን ትናንት ዐሳውቆ ነበር ።

ናይሮቢ፥ አድማ የመቱ የናይሮቢ አየር መንገድ ሠራተኞች ወደ ሥራ ገበታቸው ለመመለስ ተስማሙ

በኬንያ መዲና ናይሮቢ የሚገኘዉ ጆሞ ኬንያታ ዓለም አቀፍ አውሮፕላን ማረፊያ ዛሬ አድማ የመቱ ሠራተኞች ወደ ሥራ ገበታቸው ለመመለስ ተስማሙ ። ይህንንም የኬንያ የሠራተኞች ማኅበር ማሳወቁን ሮይተርስ ዘግቧል ። ሠራተኞቹ ዛሬ በመቱት የሥራ ማቆም አድማ ወደ ኬንያ መዲና የሚደረጉ በረራዎችን አስተጓጉሏል ። የኢትዮጵያ አየር መንገድን ጨምሮ የተለያዩ አየር መንገዶች መነሻና መዳረሻቸውን ናይሮቢ ያደረጉ በረራዎች በጊዜያዊነት ማቋረጣቸውን ቀደም ሲል ገልጠዋል ። ሠራተኞቹ አድማዉን የመቱት የኬንያ መንግሥት ከማእድን ነጋዴው የህንዱ አዳኒ ኩባንያ ጋር ያቀደውን ስምምነት በመቃወም ነዉ ።  ስምምነቱ የጆሞ ኬንያታ ዓለም አቀፍ አውሮፕላን ማረፊያን ማደስና አዲስ መተላለፊያና ማረፊያ መገንባትne ያካትታል ። በስምምነቱ መሠረት አዳኒ የተባለዉ የህንዱ ኩባንያ የኬንያ ዋና የአውሮፕላን ማረፊያን ለ30 ዓመታት ያስተዳድራልም ተብሏል ። አድማዉን የመቱት የጆሞ ኬንያታ አዉሮፕላን ማረፍያ ሠራተኞች ስምምነቱ ከሥራ መባረርን ያስከትላል የሥራ ሁኔታዉንም የከፋ ያደርጋል ሲሉ ስጋታቸዉን ገልጠዋል ።

ፊላዴልፊያ፥ የዩናይትድ ስቴትስ ኡጩ ፕሬዚደንቶች በቴሌቪዥን ተከራከሩ

የዩናይትድ ስቴትስ ሁለቱ የዘንድሮ እጩ ፕሬዚደንት ተፎካካሪዎች ፊላዴልፊያ ውስጥ ለመጀመሪያ ጊዜ ፊት ለፊት በአካል ተገኝተው በቴሌቭዥን ተከራከሩ ። የዴሞክራቶቹ ተወካይ ምክትል ፕሬዚደንት ካማላ ሐሪስ እና ሪፐብሊካኑ የቀድሞው ፕሬዚደንት ዶናልድ ትራምፕ በበርካታ ጉዳዮች ላይ ለ90 ደቂቃ ብርቱ ክርክር አድርገዋል ። በውርጃ፤ በኤኮኖሚ፤ በፍልሰተኞች እና በውጭ ጉዳይ ፖሊሲ ላይ በብርቱ ተሟግተዋል ። ካማላ ሐሪስ በማክሰኞው ምሽት ክርክር ተፎካካሪያቸው ዶናልድ ትራምፕ ተከላካይ እንዲሆኑ ማስገደዳቸውን ተንታኞች ገልጠዋል ። ከክርክሩ በኋላ መራጮች የተለያዩ አመለካከቶቻቸውን አንጸባርቀዋል ።  ስማቸው ያልተጠቀሰ አንድ የሪፐብሊካን ደጋፊ የዶናልድ ትራምፕ አሸናፊነትን እንደሚፈልጉ ተናግረዋል። 

«በዚህ ምርጫ ፕሬዚደናት ዶናልድ ትራምፕን ነው የምደግፈው ። ምክንያቱም በ2016 ያመጡልን እና ለአራት ዓመታት ያደረጉልን ራሱ እንዲደገም እንሻለን ።  ጠንካራ ኤኮኖሚ ያስፈልገናል ። ለዓለም ሰላም፥ ለእያንዳንዱ ሰውም ብልጽግና ያሻናል ። »

የምርጫ ክርክሩን በቴሌቪዥን ያደመጡ የዴሞክራቶች ደጋፊ በበኩላቸው የካማላ ሐሪስ ወደፊት በፕሬዚደንትነት መመረጥ ትርጉሙ ላቅ ያለ እንደሆነ ገልጠዋል። 

«የእሳቸው መታጨት እና ፕሬዚደንት መሆን ለአጠቃላዩ ትውልድ በሚገርም ሁኔታ አነቃቂ ይሆናል ።  በአስቸጋሪ ሁኔታ ውስጥ መረጋጋትን ብሎም ለፖለቲካው ስክነት አምጥተዋል ።»

ፕሬዚደንት ዶናልድ ትራምፕ ዛሬ ማለዳ ከፎክስ ቴሌቪዥን ጋ ባደረጉት ቃለመጠይቅ በኤቢሲ (ABC)ቴሌቪዥን ምሽቱን የተላለፈው ክርክር እሳቸውን የተጫነ እና ለተፎካካሪያቸው ያደላ መሆኑን በመግለጥ አማreረዋል ። እሳቸው ሲናገሩ በጋዜጠኞቹ እርምት ሲሰጥ እንደነበር፤ ተፎካካሪያቸው ግን ችላ ተብለው እንደታለፉም በመግለጥ ወቅሰዋል ። ክርክሩን የታደሙ በርካቶች እንደሚሉት የሕግ አዋቂዋ ካማላ ሐሪስ ፖሊሲዎች ላይ ሲያተኩሩ ዶናልድ ትራምፕ አብዛኛውን ጊዜ በወቀሳ እና ያለፉ ጉዳዮችን በማንሳት ማማረራቸውን ጠቅሰዋል ። ክርክሩ ስምንት ሳምንት ግድም በቀረው የዩናይትድ ስቴትስ የፕሬዚደንት ምርጫ በተለይ ባልወሰኑ መራጮች ላይ ተጽእኖ እንደሚኖረው ተገልጧል ።

ሐኖይ፥ ቬትናም ውስጥ አውሎ ንፋስ በርካቶችን ገደለ

ቬትናም ውስጥ «ያጊ» የሚል ስያሜ የተሰጠው ብርቱ አውሎ ነፋስ ካለፈ በኋላ የሞቱ እና የጠፉ ሰዎች ቁጥር እየጨመረ ነው ። የሀገሪቱ የአደጋ መቆጣጠሪያ እንዳለው ከሆነ በአውሎ ንፋሱ ጥፋት ቢያንስ 143 ሰዎች ሞተዋል ።  58 ሰዎች ደግሞ አሁንም ያሉበት ዐይታወቅም ። በዐሥርተ ዓመታት ውስጥ እጅግ በጣም ኃይለኛ የተባለለት ሞቃታማው አውሎ ንፋስ በሳምንቱ መጨረሻ በተለይም በደቡብ ምስራቅ እስያ ሰሜናዊ ክፍል ተቀስቅሷል ። አውሎ ንፋሱ ባደረሰው አደጋ ከ800 በላይ ሰዎች ቆስለዋል ። እንደ ሀገር ውስጥ የአደጋ መቆጣጠሪያ ጥበቃ ከሆነ፦ አውንፋሱ ከ100,000 በላይ ቤቶችን አውድሟል ። በርካቶች በውኃ ተከበው ይገኛሉ ። ብርቱው ዝናብ በቀጠለ ቁጥር ከ20 ዓመታት ወዲህ ታይቶ በማይታወቅ መልኩ የወንዞች ሙሌት መጠንም እየጨመረ ነው ። በቀይ ወንዝ ሙሌት የተነሳም ዋና ከተማዋ ሐኖይ ውስጥ ያሉ ነዋሪዎች ለደኅንነታቸው ሲባል ወደ ሌሎች አጎራባች ቦታዎች ተወስደዋል ።  

ቀጣዩን ክፍል ዝለለዉ ስለዚሕ ዝግጅት

ስለዚሕ ዝግጅት

PODC-DW-Amharisch-News-DWcom

የዓለም ዜና

ዶይቼ ቬለ የዕለቱን ዋና ዋና የዜና ትንታኔዎች ከኢትዮጵያ እና ከመላው ዓለም በየቀኑ ያቀርባል። የኢትዮጵያ እና የአፍሪካ ፖለቲካዊ እና ኤኮኖሚያዊ ጉዳዮችን ጨምሮ የመላው ዓለምን ውሎ የተመለከቱ ጠቃሚ መረጃዎች በሰባቱም የሣምንቱ ቀናት ከምሽቱ አንድ ሰዓት ከዶይቼ ቬለ ያድምጡ።